SelamAbesha.com

                

የኢትዮ-አሜሪካ የሁለትዮሽ ትብበር ይበልጥ እየተጠናከረ መምጣቱ ተገለፀ

የኢትዮ-አሜሪካ የሁለትዮሽ ትብበር ይበልጥ እየተጠናከረ መምጣቱ ተገለፀ

አዲስ አበባ ነሃሴ 17/2008 ኢትዮጵያና አሜሪካ በልማት፣በፀጥታና ሌሎች ጉዳዮች ያላቸው የሁለትዮሽ ትብብር ይበልጥ እየተጠናከረ መምጣቱ ተገለጸ።


ፕሬዝዳንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመ የስራ ጊዜያቸውን ያጠናቀቁትን በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ፓትሪሺያ ሃስላችን ዛሬ አሰናበቱ።


አምባሳደር ፓትሪሺያ በሶስት ዓመታት የኢትዮጵያ ቆይታቸው ለሁለቱ አገራት ትብብር መጠናከር ላበረከቱት አስተዋጽኦም ፕሬዝዳንቱ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።


ውይይቱን የተከታተሉት በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአሜሪካ ጉዳዮች ዳይሬክተር አቶ መክብብ መንገሻ የአካባቢ ጸጥታንና ሰላም ማስከበር  እንዲሁም የልማት ትብብሩን ይበልጥ ማጠናከር የውይይታቸው አጀንዳ ነበር።


የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን በጋራ ለመስራት የሚያስችላቸውን ውይይትም አድርገዋል።


ሁለቱ አገሮች በተለይ በኢንቨስትመንት ዘርፍ ያላቸው ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር እንደሚሰሩም አረጋግጠዋል።


የአሜሪካው ፕሬዝዳንት በኢትዮጵያ ያደረጉት ጉብኝት የሁለትዮሽ ግንኙነቱ እያደገ መምጣቱን የሚያመላክትና ይበልጥ የሚያነቃቃ መሆኑንም ጠቁመዋል።


አሜሪካ ከምታደርገው የልማት ትብብር ባሻገር በአሁኑ ወቅት በተከሰተው ድርቅ የሰብዓዊነት እርዳታ ማድረጓንም ፕሬዝዳንት ሙላቱ አድንቀዋል።


በቀጣይም ሁለቱ አገራት በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተባብረው መስራት የሚችሉበት ሁኔታ እየሰፋ መምጣቱ ተገልጿል።


አምባሳደር ፓትሪሺያ ሃስላች በበኩላቸው እስካሁን በኢትዮጵያ በነበራቸው ቆይታ መደሰታቸውን ተናግረዋል።


የሁለቱን አገራት ግንኙነት ለማጠናከርና ተልዕኳቸውን ለመፈጸም እንዲችሉ በኢትዮጵያ ለተደረገላቸው ድጋፍና ትብብርም አመስግነዋል።


የሁለቱ አገራት ግንኙነት በኢትዮጵያ የትምህርት ስርዓት ለማስፋፋትና ጠንካራ የሰው ኃይል ለማፍራት እንዲሁም በሰብዓዊነት እርዳታ ሳቢያ ነበር በ1903 ዓ.ም የጀመረው።


የደርግ መንግስት ስልጣን ላይ መውጣቱን ተከትሎ የሁለቱ አገሮች ግንኙነት ተቀዛቅዞ የነበረ ቢሆንም ከስርዓቱ ውድቀት በኋላ ግን ዳግም እያንሰራራ መጥቷል።


Selamabesha.com

Hosted By Fissha Belay

© COPYRIGHT. ALL RIGHTS RESERVED